EthiopiaNews

የበይነ መረብ መገናኛ ብዙሃን

በኢትዮጵያ ህጋዊ ፈቃድ ያላቸው 73 የበይነ መረብ መገናኛ ብዙሀን እንደሚገኙ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሀን ባለስልጣን አስታውቋል።

ይህ የተገለፀው የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን “ብቃት ያለው የበይነ መረብ መገናኛ ብዙኃን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም” በሚል መሪ ሀሳብ ባካሄደው የውይይት መድረክ ላይ ነው።

በዚሁ ጊዜም የበይነ መረብ መገናኛ ብዙሀን የሀገሪቱን ሕግ፣ የጋዜጠኝነት የሙያ ሥነ-ምግባርን በማክበር ለሰላም፣ ለአንድነትና ለብሔራዊ ጥቅም መከበር አበክረው ሊሰሩ እንደሚገባ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኃይማኖት ዘለቀ ገልፀዋል።

የበይነ መረብ መገናኛ  ብዙኃን  ለሕዝብ  ወቅታዊና ትክክለኛ  መረጃ በማቅረብ ፣ በሰላም፣ በልማት እንዲሁም  የህብረተሰቡን  አመለካከት  በመቅረፅ፤ በሀገር ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና  ማህበራዊ  ዕድገት ውስጥ የበኩላቸውን  ገንቢ  ሚና የሚጫወቱ ተቋማት  መሆን እንዳለባቸውም በመድረኩ ተገልጿል።

በመሆኑም መገናኛ ብዙሃኑ የጋዜጠኝነት ሙያዊ መርህን በመከተል ሊሰሩ እንደሚገባ ያመለከቱት ዋና ዳይሬክተሯ ከሀሰተኛ መረጃና ጥላቻ ንግግር ሥርጭት በመቆጠብ ለህዝቦች አንድነትና ትስስር መጠናከር ሊሰሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ዘነበ ሃይሉ ነው የዘገበው፡፡