EthiopiaNews

ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ

ሀገራዊ ምክክርን ወደ ታሪካዊ ምዕራፍ ያሸጋግራል የተባለለት ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ከሐምሌ 8 ጀምሮ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ተነግሯል።

የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ይህ ቀን  ላለፉት አራት ዓመታት ሲያከናውናቸው የቆየውን ሰፊ የምክክር ሂደቶች አጠናቆ ወደ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ የተሸጋገረበት መሆኑን አሳውቋል።

በዚህም መሠረት የመጀመሪያው ዙር ሀገራዊ ምክክር ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ እንደሚጀመርና ለሦስት ተከታታይ ሳምንታት እንደሚቆይም ታውቋል።

የምክክሩ ተሳታፊዎች ደግሞ ከመላው ኢትዮጵያ ከምክክሩ አንድ ሳምንት ቀድመው በአዲስ አበባ ይከትማሉ ነው የተባለው።

ኮሚሽኑ ባለፉት አራት ዓመታት በነበሩት የምክክር ሂደቶች ውስጥ በርካታ ውስብስብ ፈተናዎች ቢያጋጥሙትም፣ እነዚህን ተግዳሮቶች በሕዝቡና በባለድርሻ አካላት መካከል በነበረው ጠንካራ የአብሮነትና የጽናት መንፈስ ማለፍ እንደተቻለም ገልጿል።

የምክክር ሂደቱ ፍጹም አካታችና አሳታፊ እንዲሆን በተደረገው ከፍተኛ ጥረት እጅግ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ያመለከተው ኮሚሽኑ፣ በ12 ክልሎች በሚገኙ 1,234 ወረዳዎች ላይ ሰፊ የምክክር መድረኮችን ማካሄድ እንደተቻለ አስታውቋል።

ይህም በአጠቃላይ ሲሰላ 93 በመቶ የሚሆነውን የሀገሪቱን ክፍል ተደራሽ ያደረገ ሰፊና ታሪካዊ የሕዝብ ተሳትፎ ሽፋን የተረጋገጠበት እንደሆነም በመግለጫው ተብራርቷል።

በሐምሌ 8ቱ ታሪካዊ ጉባኤ ላይ የሚሳተፉ የኅብረተሰብ ክፍሎች በሀገሪቱ መሠረታዊና ስትራቴጂካዊ አጀንዳዎች ላይ በሰለጠነ መንገድ፣ በውይይትና በሃሳብ የበላይነት ላይ ተመስርተው እንዲመክሩ ይጠበቃልም ተብሏል።

ይህም በዋናነት በሕዝቦች መካከል ያለውን ግንኙነትና ትስስር ለማሻሻል እንዲሁም በሁሉም ዘንድ ቅቡልነት ያለው ጠንካራ ሀገረ መንግሥት ለመመሥረት ትልቅ መሠረት እንደሚጥል ነው የተነገረው።

ይህ ለአራት ዓመታት የተደከመበት የምክክር ጉባኤ በተሳካ ሁኔታ እንዲካሄድ ሰፊ የሎጅስቲክስ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን የጠቆመው ኮሚሽኑ፣ የጉባኤው ተሳታፊዎች አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት አጠናቀው ከጉባኤው መጀመርያ ቀን አንድ ሳምንት ቀድመው ወደ አዲስ አበባ እንዲገቡ እንደሚደረግ አስታውቋል።

ኮሚሽኑ ዝግጅቱን ባበሰረበት በዚህ ታሪካዊ ወቅት፣ እስካሁን ድረስ በተለያዩ ምክንያቶች በሂደቱ ውስጥ ላልተሳተፉ ወገኖች በሙሉ ጥሪ አቅርቧል።

እነዚህ ወገኖች ወደ ምክክር መድረኩ በመምጣት የሀገራቸውን መፃኢ ዕድል በጋራ ውይይት እንዲወስኑ ኮሚሽኑ አገራዊና ታሪካዊ ጥሪውን በድጋሚ አስተላልፏል።

#EBS

#EBSTVNEWS

#EBSTVSPORT

#_7696_WN

https://t.me/ebstvnews

www.ebstv.tv