LatestNews

የውጭ ሀገር ገንዘብና የጦር መሳሪያ ሲያዘዋወሩ የተገኙ አምስት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ዋሉ

የጋምቤላ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ከ300 ሺህ በላይ የውጭ ሀገር  ገንዝብ እና  ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ሲያዘዋውሩ የተገኙ አምስት ተጠርጣሪዎችን  በቁጥጥር ሥር ማዋሉን   አስታወቀ።

የክልሉ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር ቱት ኮር ለኢዜአ እንደገለጹት ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር የዋሉት  ከህብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ  ባለፉት ሶስት ቀናት ውስጥ በጋምቤላ ከተማ፣ ዲማና ኢታንግ ወረዳዎች በተደረገው ክትትል ነው።

በዚህም ከ300 ሺህ በላይ የደቡብ ሱዳን “ፎን” ገንዘብ ፣ሶስት የክላሽንኮቭ እና አንድ ብሬን ጠብንጃዎች፣ አንድ ሽጉጥ እንዲሁም 90 የብሬንና ዲሽቃ ተተኳሽ ጥይቶች ከተጠርጣሪዎቹ እጅ መገኘታቸውን አስታውቀዋል።

ተጠርጣሪዎች በአሁኑ ወቅት በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን እየተደረገባቸው ያለው የምርመራ ሂደት እንደተጠናቀቀም ጉዳያቸው ወደ ፍርድ ቤት የሚላክ ይሆናል ብለዋል።

ኮሚሽኑ ባለፉት ስድስት ወራት ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውርን ለመግታት  ባደረገው ጥረት 315 የክልሸንኮቭ እና ሁለት የብሬን ጠብንጃዎች እንዲሁም  አንድ ሺህ 790  የተለያዩ ተተኳሽ ጥይቶችን በቁጥጥር ስር መዋሉንም አውስተዋል።

የህዝቡን ተሳትፎ በማጠናከር ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውሩን ለማግታት የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ  ኢዜአ ዘግቧል።