በሀገራዊ የምክክር ጉባኤ መግባባት ላይ የተደረሰባቸው ሀሳቦች የኢትዮጵያን ውስብስብ ችግሮች የሚፈቱ ናቸው ሲል የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ገለጸ፡፡
የፓርቲው ሊቀመንበር ሙሉዓለም ተገኘወርቅ በዛሬው ዕለት በሰጡት መግለጫ ኢዜማ በሀገራዊ ምክክሩ ለጠቅላላ ጉባኤ የቀረቡ ስምንቱ አጀንዳዎች እና የውሳኔ ሀሳቦችን እንደሚቀበል ገልጸል፡፡
የሀገራዊ ምክክሩ ሂደት ውስብስብ ችግሮችን በጠረጴዛ ዙሪያ በምክክር ለመፍታት አዲስ በር የሚከፍት ስለመሆኑ አንስተው፤ ኢዜማ በሀገራዊ ምክክሩ ከጅምሩ እስከ ፍጻሜው ንቁ ተሳትፎ ማድረጉንም ነው የገለጹት፡፡
በምክክሩ መግባባት ላይ የተደረሰባቸው አጀንዳዎች ለህዝብና ለመንግስት የሚቀርቡበት የትግበራ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ኢዜማ ድጋፉን እንደሚቀጥል አመልክተዋል፡፡
በምክክሩ መግባባት ላይ የተደረሰባቸው ሀሳቦች ትግበራ አስፈላጊውን ሂደት የተከተለ እንዲሆንም ፓርቲው አጽንኦት ሰጥቷል፡፡
ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም መካሄድ የጀመረው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመዝጊያ ሥነ ሥርዓት ባሳለፍነው ነሐሴ 16 ቀን 2018 ዓ.ም መካሄዱ ይታወሳል፡፡
