የሃይማኖት ጉዳዮች እና የሰላም ግንባታ አጀንዳዎች ተመካካሪዎች ባቀረቧቸው ምክረ ሃሳቦቻቸው መግባባት ላይ መድረሳቸውን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አስታወቀ።
ኮሚሽኑ ከሐምሌ 8/2018 ዓ.ም ጀምሮ እያካሄደ ባለው የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ በኮሚሽኑ ምክር ቤት በተለዩ ስምንት አጀንዳዎች ላይ ምክክር እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል፡፡
አጀንዳዎቹ 500 አባላት ባሏቸው ስምንት የስራ ቡድኖች ምክክር እየተደረገባቸው እንደሚገኙ ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡
በኮሚሽኑ የአሰራር ሥነ-ዘዴ መሰረት 500 አባላት ያሉት አንድ ቡድን በአንድ አጀንዳ ላይ እየተመካካረ ይገኛል፡፡
ኮሚሸኑ ባወጣው መግለጫ በሃይማኖት ጉዳዮች እና በሰላም ግንባታ አጀንዳዎች ላይ ሲመካካሩ የቆዩት ሁለት ቡድኖች ዛሬ ነሐሴ 5/2018 ዓ.ም በተጠናቀሩ ምክረ ሃሳቦቻቸው ላይ ተስማማተው በተዘጋጀው ቃለ ጉባኤ ላይ ተፈራርመዋል፡፡
የሌሎች አጀንዳዎች ተመካካሪዎችም በቀጣይ ቀናት በተመሳሳይ መልኩ የአጀንዳ ሃሳቦቻቸውን የጋራ አድርገው በቃለ ጉባኤዎቻቸው ላይ በመፈራረም እንደሚስማሙ ይጠበቃል፡፡
